በየዓመቱ Cambridge የተመጣጠነ በጀት የምታጸድቅ ሲሆን፣ ይህም ማለት የከተማ አስተዳደሩ ያቀደው ወጪ ሊያገኘው ከሚጠብቀው ገቢ ጋር እኩል መሆን አለበት።
እንደአብዛኞቹ ማዘጋጃ ቤቶች፣ የንብረት ግብር ለዚህ የገንዘብ ምንጭ ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳል። ነገር ግን የከተማ አስተዳደሩ ነዋሪዎች በየዕለቱ የሚጠቀሟቸውን አገልግሎቶች ለመሸፈን የአገልግሎት ክፍያዎችን፣ የክልልና የፌዴራል መንግሥት የገንዘብ ድጋፎችን፣ ከፈቃዶችና ከማስፈቀጃዎች የሚገኙ ገቢዎችን እንዲሁም ከኢንቨስትመንት የሚገኙ ትርፎችን ጨምሮ ሌሎች በርካታ የገቢ ምንጮችን ይጠቀማል።
የተለያዩ የገቢ ምንጮችን መጠቀም በንብረት ግብር ላይ ያለውን ጥገኝነት ለመቀነስ የሚረዳ ሲሆን፣ ትምህርት ቤቶችን፣ የሕዝብ ደህንነትን፣ መሠረተ ልማቶችን፣ ቤተ መጻሕፍትን፣ ፓርኮችን እና ሌሎች በርካታ የማኅበረሰብ አገልግሎቶችን ለመደገፍ የሚያስፈልጉ ሀብቶችን ለማሟላት ያስችላል።
የንብረት ግብርን መረዳት
የአንድን ንብረት ዓመታዊ የግብር ክፍያ መጠን የሚወስኑ በርካታ ምክንያቶች አሉ።
የከተማ አስተዳደሩ ዓመታዊ በጀት የንብረት ግብር ገቢው ምን ያህል መስተካከል እንዳለበት ይወስናል። በመቀጠል የንብረቶች ዋጋ በከተማው የምዘና ሂደት በገለልተኝነት የሚወሰን ሲሆን፣ በMassachusetts Department of Revenue (የMassachusetts የገቢ መምሪያ) ይረጋገጣል። በመጨረሻም የክልሉ ሕግ Cambridge በንብረት ግብር ምደባ ሥርዓት አማካኝነት ለመኖሪያ እና ለንግድ ንብረቶች የተለያዩ የግብር ተመኖችን እንድትጠቀም ይፈቅዳል።
የከተማ አስተዳደሩ በንብረቶች ዋጋ ላይ የሚከሰቱ ለውጦችን መቆጣጠር ባይችልም፣ በየዓመቱ መሰብሰብ ያለበትን የንብረት ግብር መጠን፣ በበጀት ዝግጅት ሂደቱ ወቅት መወሰን ይችላል።
የCambridge ከተማ ጠንካራ የፋይናንስ መሠረት እንዲኖራት ካደረጉ ዋና ዋና ምክንያቶች አንዱ ከፍተኛ የግብር ገቢ የሚያመነጩ በርካታ የንግድ ተቋማት የሚገኙበት ቦታ መሆኗ ነው። የንግድ ንብረቶች በአካባቢው ከፍተኛውን የንብረት ግብር የሚከፍሉ ሲሆን፣ ይህም የከተማ አስተዳደሩን አገልግሎቶች ለመደገፍ እንዲሁም በመኖሪያ ንብረት ባለቤቶች ላይ ያለውን የግብር ጫና ለመቀነስ ይረዳል።
በዚህም ምክንያት Cambridge በGreater Boston አካባቢ የመኖሪያ ቤት ባለቤቶች ላይ አነስተኛ የግብር ጫና ከሚጥሉ ከተሞች መካከል አንዷ ሆና ቀጥላለች።
የከተማዋ የገቢ ምንጮች
ከንብረት ግብር የሚሰበሰበው ገቢ የከተማዋ ዋና የገቢ ምንጭ ቢሆንም፣ Cambridge የከተማ አስተዳደሩን ሥራዎች የሚያስኬዱ ሌሎች ተጨማሪ የገቢ አማራጮች አሏት። እነዚህም የአገልግሎት ክፍያዎችን፣ የቅጣትና የውርስ ንብረት ገቢዎችን፣ ከመንግሥታዊ ተቋማት የሚገኙ ድጋፎችን፣ የፈቃድ ክፍያዎችን እንዲሁም ልዩ ልዩ ገቢዎችን ያካትታሉ።
ግብር — $758.8 ሚሊዮን
የንብረት ግብር የከተማዋ ዋነኛ የገቢ ምንጭ ነው። ከዚህ በተጨማሪ የከተማው አስተዳደር ከሌሎች የግብር ምንጮች እንዲሁም ከግብር ነፃ የመሆን መብት ከተሰጣቸው የንብረት ባለቤቶች በፈቃደኝነት ከሚከፈሉ Payments in Lieu of Taxes (PILOT፣ በፈቃደኝነት በግብር ምትክ የሚከፈል ክፍያ) ገቢ ያገኛል።
ከአገልግሎት ክፍያዎች — $107.2 ሚሊዮን
በአገልግሎት ተጠቃሚዎች የሚከፈሉ ክፍያዎች እንደ መዝናኛ ፕሮግራሞች ያሉ፣ ግለሰቦች በቀጥታ ተጠቃሚ የሚሆኑባቸውን አገልግሎቶች ለመደገፍ ይውላሉ።
ከመንግሥት አካላት የሚገኝ ገቢ — $62.8 ሚሊዮን
የፌዴራልና የክልል ድጎማዎች፣ የክልል ዕርዳታ እና ሌሎች ከመንግሥት የሚገኙ የገንዘብ ድጋፎች የተለያዩ የከተማ አስተዳደሩ ፕሮግራሞችንና አገልግሎቶችን ለመርዳት ያግዛሉ።
ልዩ ልዩ ገቢዎች — $56 ሚሊዮን
ይህ ምድብ ከኢንቨስትመንት የሚገኝ ገቢን፣ ከሌሎች ፈንዶች የሚደረጉ የገንዘብ ዝውውሮችን እና የከተማ አስተዳደሩን ሥራዎች ለመደገፍ የሚውሉ ሌሎች የተለያዩ የገቢ ምንጮችን ያካትታል።
ፈቃዶችና ፈቃድ መስጫዎች — $37.6 ሚሊዮን
ከፈቃዶችና ከማስፈቀጃ ሂደቶች የሚገኘው ገቢ የሕንፃ፣ የእሳት አደጋ እና የንግድ ፈቃዶችን ጨምሮ የከተማውን ደንቦች ለማስፈጸምና ሥራዎችን ለማስኬድ ያግዛል።
ቅጣቶችና የተወረሱ ንብረቶች — $10.8 ሚሊዮን
ከፓርኪንግ ጥሰቶችና ከሌሎች የማዘጋጃ ቤት ቅጣቶች የሚገኘው ገቢ የከተማ አስተዳደሩን ሥራዎች ለመደገፍ የሚያግዝ ሲሆን፣ የአካባቢው ሕጎችና ደንቦች እንዲከበሩ ያበረታታል።
የንብረት ግብርን በተቻለ መጠን ዝቅተኛ ማድረግ
Cambridge ተግባራዊ በሆነበት አጋጣሚ ሁሉ ከንብረት ግብር ውጭ ያሉ ገቢዎችን በተቻለ መጠን ለማሳደግ የሚረዱ አማራጮችን አሁንም እየፈለገች ትገኛለች።
ለአገልግሎቶች ተገቢ ክፍያዎችን በመሰብሰብ፣ ፈቃዶችንና ማስፈቀጃዎችን በአግባቡ በማስፈጸም፣ ከክልልና ከፌዴራል መንግሥት የሚገኙ የገንዘብ ድጋፎችን በመጠቀም እና የከተማ አስተዳደሩን ሀብቶች በኃላፊነት በማስተዳደር፣ Cambridge በንብረት ግብር ላይ ብቻ የሚኖረውን ጥገኝነት ታቃልላለች።
በFY27 ከተማ አስተዳደሩ የሚሰበስበው ጠቅላላ የንብረት ግብር፣ ከFY26 ጋር ሲነፃፀር በ6.9 በመቶ ወይም በ$46.8 ሚሊዮን ዶላር እንደሚጨምር ይገመታል። እነዚህ ገቢዎች በዚህ ዓመት በጀት ውስጥ የተካተቱትን አገልግሎቶች፣ መሠረተ ልማቶችን እና ኢንቨስትመንቶችን ለመደገፍ ይውላሉ።
የከተማ አስተዳደሩ የነዋሪዎችን የግብር ጫና ለማቃለል ከንብረት ግብር ውጭ ያሉ የገቢ ምንጮችን የማሳደግ ፖሊሲውን ያስቀጠለ ሲሆን፣ ለዚህም የፈቃድ አሰጣጥ ደንቦችን በማስፈጸም፣ ከአገልግሎት ተጠቃሚዎች ክፍያ በመሰብሰብ እና ውዝፍ የፓርኪንግ ቅጣቶችን በማስከፈል የገቢ ምንጮችን ማሳደግ ችሏል። ከንብረት ግብር ውጭ ያሉ በርካታ ዋና ዋና የገቢ ምንጮች፣ የንብረት ግብርና የንብረት ምደባ ሂደት አካል በሆነው በፎል ወቅት እንደገና ይገመገማሉ።