የFY27 ሥራ ማስኬጃ በጀት ከአለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ4.1% አድጓል። ይህ በግምት የ$41 ሚሊዮን ዶላር ጭማሪ ያለው ቢሆንም፣ Cambridge ባለፉት 5 እና 10 ዓመታት ካሳየችው አማካይ የበጀት እድገት በእጅጉ ያነሰ ነው።
አብዛኛው የበጀቱ ጭማሪ ነዋሪዎች የሚጠብቁትን ጥራት ያለው አገልግሎት ለማስቀጠል እና ማኅበረሰቡን በሚያጠናክሩ ቅድሚያ በሚሰጣቸው ጉዳዮች ላይ ኢንቨስት ማድረግን ለመቀጠል ከሚያስፈልጉ ወጪዎች መጨመር ጋር የተያያዘ ነው።
በትምህርት ላይ የሚደረግ ኢንቨስትመንት
ከፍተኛው የበጀት ጭማሪ በግምት $13.3 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ሲሆን፣ ለCambridge Public Schools ድጋፍ ያደርጋል። ይህ የገንዘብ ድጋፍ ትምህርት ቤቶች ለCambridge ሕጻናት ከፍተኛ ጥራት ያለው ትምህርት፣ የተማሪዎች ድጋፍ እና የመማር ዕድሎችን ማቅረባቸውን እንዲቀጥሉ ያግዛል።
የከተማዋን የሥራ ኃይል መደገፍ
በመላ አገሪቱ እንዳሉ ሌሎች አሠሪዎች ሁሉ፣ Cambridgeም እየጨመረ የመጣውን የሠራተኞች ወጪ እያስተናገደች ትገኛለች። የFY27 በጀት የደመወዝ ጭማሪን፣ የሠራተኞች ጥቅማጥቅሞችን እና የ2.5 በመቶ የኑሮ ውድነት ማስተካከያን ጨምሮ ወደ $21 ሚሊዮን ዶላር የሚጠጋ ተጨማሪ በጀት ለከተማዋ ሠራተኞች መድቧል። እነዚህ ኢንቨስትመንቶች ከተማዋ አስፈላጊና ውጤታማ የሆኑ የሕዝብ አገልግሎቶችን ለማቅረብ የሚያስፈልጉ ብቁ ሠራተኞችን ለመቅጠርና በሥራ ላይ ለማቆየት ያስችሏታል።
ወሳኝ መሠረተ ልማቶችን መንከባከብ
በጀቱ በተጨማሪም የዕለት ተዕለት ኑሮን የሚደግፉ መሠረተ ልማቶችን ለመጠበቅና ለመንከባከብ የሚወጣው ወጪ እየጨመረ መምጣቱን ያንጸባርቃል።
ከረጅም ጊዜ የካፒታል ኢንቨስትመንቶች ጋር የተያያዘው የዕዳ ክፍያ በ$4.7 ሚሊዮን ዶላር ያደገ ሲሆን፣ ለMassachusetts Water Resources Authority (MWRA) የሚከፈሉ ክፍያዎችም በግምት በ$1.2 ሚሊዮን ዶላር ጨምረዋል። እነዚህ ኢንቨስትመንቶች አስተማማኝ የውኃ እና የፍሳሽ ማስወገጃ ሥርዓቶችን ለመጠበቅ፣ እንዲሁም በሕዝብ ተቋማትና መሠረተ ልማቶች ላይ የሚደረጉ ማሻሻያዎችን አጠናክሮ ለመቀጠል ያግዛሉ።
የማኅበረሰቡን ፍላጎቶች ማሟላት
የFY27 በጀት እየተለዋወጡ የሚመጡ የማኅበረሰቡን ፍላጎቶች መሠረት ያደረጉ ኢንቨስትመንቶችን ያካተተ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል፦
- $1.3 ሚሊዮን ዶላር ለውኃ ማጣሪያ ዕቃዎች
- $1 ሚሊዮን ዶላር የከተማውን የመኖሪያ ቤት ድጎማ ቫውቸዎሮች ለማስፋፋት
- $1 ሚሊዮን ዶላር ልዩ ዝግጅቶችን ለመደገፍ
- $500,000 ዶላር የበረዶ ማስወገድ ሥራዎችን ለመደገፍ
- ተጨማሪ የገንዘብ ድጋፍ ለሠራተኞች ሥልጠና እና የትምህርት ወጪ ክፍያን ለመሸፈን
- በችግር ጊዜ የሚሰጡ የአስቸኳይ ድጋፎችና የሕክምና አገልግሎቶችን መደገፍ
- ለአረጋውያን የሚሆኑ ተጨማሪ የምግብ ፕሮግራሞች
- በከተማዋ መሥሪያ ቤቶች የሚታዩ መደበኛ የውልና የሥራ ማስኬጃ ወጪ ጭማሪዎች
እያንዳንዱ በጀት እየጨመሩ ባሉ ወጪዎች እና ማኅበረሰቡ ቅድሚያ በሚሰጣቸው ጉዳዮች መካከል ያለውን ሚዛን የሚያንጸባርቅ ነው። የFY27 በጀት የከተማውን ጥንቃቄና ኃላፊነት የተሞላበት የፋይናንስ አስተዳደር አቋም ሳያጓድል፣ በትምህርት፣ በመሠረተ ልማት፣ በሕዝብ አገልግሎቶች እና ነዋሪዎችን በሚደግፉ ፕሮጀክቶች ላይ ኢንቨስት ማረጉን ቀጥሏል።