የከተማው የሥራ ማስኬጃ በጀት Cambridge በየዕለቱ ያለአንዳች እንቅፋት እንድትቀጥል ለሚያስፈልጉት ሰራተኞች፣ ፕሮግራሞች እና አገልግሎቶች የሚሆን ወጪን ይሸፍናል።
የሥራ ማስኬጃ በጀቱ የከተማዋ መሥሪያ ቤቶች ዓመቱን ሙሉ ለማኅበረሰቡ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስፈልጋቸውን የገንዘብ ድጋፍ ያቀርባል። ይህም ሕፃናትን ከማስተማርና መንገዶችን ከመንከባከብ ጀምሮ፣ ለአስቸኳይ ሁኔታዎች ምላሽ መስጠትን፣ ቤተሰቦችን መደገፍን፣ ቤተ-መጻሕፍትንና መናፈሻዎችን ማስተዳደርን ያካትታል።
የFY27 የሥራ ማስኬጃ በጀት በድምሩ 1.03 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን፣ ከጁላይ 1 ቀን 2026 ዓ.ም እስከ ጁን 30 ቀን 2027 ዓ.ም ላለው የበጀት ዓመት ይሠራል። ይህ በጀት ከFY26 ጋር ሲነጻጸር የ4.1 በመቶ ጭማሪ ያሳየ ሲሆን፣ ይህም ከተማ አስተዳደሩ ባለፉት አምስት ዓመታት ካስመዘገበው የ6.7 በመቶ እና ባለፉት አሥር ዓመታት ካስመዘገበው የ6.1 በመቶ አማካይ ዓመታዊ እድገት በእጅጉ ያነሰ ነው። ይህም አስተዳደሩ የበጀት ጭማሪው ከተገቢው ወሰን እንዳያልፍ እያመዛዘነ፣ ማኅበረሰቡ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን ፍላጎቶች ለመደገፍ ያለውን ጽኑ አቋም ያሳያል።
የሥራ ማስኬጃ በጀቱ በዋና ዋና የአገልግሎት ዘርፎች ላይ እንዴት እንደዋለ የሚከተለው ማጠቃለያ ያብራራል።
ትምህርት
$293.5 ሚሊዮን
ከከተማዋ የሥራ ማስኬጃ በጀት ውስጥ ትልቁ ድርሻ ለትምህርት የሚመደብ ሲሆን፣ ይህ ድርሻ Cambridge Public Schoolsን ለመደገፍ ይውላል። እነዚህ ኢንቨስትመንቶች መምህራንን እና ሰራተኞችን፣ የክፍል ውስጥ ትምህርትን፣ የተማሪዎች አገልግሎትን፣ የትምህርት ቤት ስራዎችን፣ እንዲሁም ተማሪዎችን ለስኬት ለማዘጋጀት የሚረዱ የትምህርት ፕሮግራሞችን ይደግፋሉ።
የማህበረሰብ እንክብካቤ እና ልማት
$227.0 ሚሊዮን
ይህ የበጀት መድብ ነዋሪዎች በየዕለቱ በከተማዋ ውስጥ የሚያገኟቸውን በርካታ አገልግሎቶች ይደግፋል። ይህ በጀት መንገዶችን እና የእግር መራመጃዎችን ለመጠገን፣ የመጠጥ ውሃ እና የዝናብ ውሃ ማስወገጃ ስርዓቶችን ለማስተዳደር፣ የመንገድ ዳር ቆሻሻን እና መልሰው ጥቅም ላይ የሚውሉ ቁሳቁሶችን ለመሰብሰብ፣ ፓርኮችን እና ዛፎችን ለመንከባከብ፣ የኪነ-ጥበብ እና የባህል ፕሮግራሞችን ለመደገፍ፣ እንዲሁም በአካባቢ ልማት ስራዎች ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ይውላል።
አጠቃላይ የከተማ አስተዳደር
$203.9 ሚሊዮን
እነዚህ መሥሪያ ቤቶች የከተማዋ አስተዳደር በብቃት እንዲሠራ የሚያስፈልጉ ወሳኝ አገልግሎቶችን ይሰጣሉ። ይህም የፋይናንስ አስተዳደርን፣ የሕግ አገልግሎቶችን፣ ምርጫዎችን፣ ፈቃድ መስጠትን፣ የመረጃ ቴክኖሎጂን (IT)፣ የሰው ኃይል አስተዳደርን እና እያንዳንዱን የከተማዋን መሥሪያ ቤት የሚደግፉ የዕለት ተዕለት የአስተዳደር ሥራዎችን ያካትታል።
የሕዝብ ደህንነት
$141.1 ሚሊዮን
የሕዝብ ደህንነት በጀት ለCambridge Police Department (የCambridge ፖሊስ መምሪያ)፣ Fire Department (የእሳት አደጋ መምሪያ)፣ Community Safety Department (የማኅበረሰብ ደህንነት መምሪያ) እና Department of Transportation (የትራንስፖርት መምሪያ) የገንዘብ ድጋፍ ያደርጋል። እነዚህ መሥሪያ ቤቶች ለአደጋ ጊዜ ፈጣን ምላሽ ለመስጠት፣ የትራፊክ ደህንነትን ለማሻሻል፣ ሰላማዊ ጎዳናዎችን ለማስጠበቅ፣ እንዲሁም ነዋሪዎችን፣ የንግድ ተቋማትን እና ጎብኚዎችን ከጉዳት ለመጠበቅ በቅንጅት ይሠራሉ።
የሰው ሀብት ልማት
$75.6 ሚሊዮን
ይህ በጀት በሁሉም የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ነዋሪዎችን የኑሮ ጥራት የሚያሻሽሉ ፕሮግራሞች ላይ ይውላል። ይህም ቤተ-መጻሕፍትን፣ የወጣቶችና ከትምህርት በኋላ የሚሰጡ ፕሮግራሞችን፣ ለአረጋውያን የሚደረጉ አገልግሎቶችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ የሥራ ዕድልና ክህሎት ማደራጃዎችን፣ የምግብና የቤት ዕርዳታዎችን እንዲሁም ማኅበረሰቡን የሚያጠናክሩ ሌሎች ፕሮግራሞችን ያጠቃልላል።
በመንግሥት አካላት መካከል የሚደረግ ትብብር
$76.9 ሚሊዮን
በተጨማሪም Cambridge ለነዋሪዎቿ አስፈላጊ አገልግሎቶችን ለሚሰጡ ክልላዊ ድርጅቶች እና አጋር መሥሪያ ቤቶች የፋይናንስ ድጋፍ ታደርጋለች። እነዚህም Massachusetts Water Resources Authority፣ Cambridge Health Alliance፣ Massachusetts Department of Transportation እና ሌሎች የጋራ የመንግሥት እና የትምህርት አገልግሎቶችን ያካትታሉ።
በሥራ ማስኬጃ በጀቱ ውስጥ የሚመደበው እያንዳንዱ ዶላር ነዋሪዎች በየዕለቱ የሚጠቀሙባቸውን አገልግሎቶች ለማቅረብ ይውላል። በጀቱ ተማሪዎችን ለማስተማር፣ መሠረተ ልማቶችን ለመንከባከብ፣ የሕዝብ ደህንነትን ለመጠበቅ፣ ፓርኮችን ለመንከባከብ እና ድጋፍ የሚያስፈልጋቸውን ነዋሪዎች ለመደገፍ የሚውል ሲሆን፣ ይህም የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ ጥራት ያላቸውን አገልግሎቶች ለማቅረብና ለወደፊቱም በኃላፊነት ለማቀድ ያለውን ቁርጠኝነት ያሳያል።